ግንቦት 4 ቀን 2014 ዓ.ም አዲስ አበባ
ቡና ባንክ በጭነት እና ህዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርት ዘርፍ ላይ ለተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ያዘጋጀውና ላለፉት ወራት ሲያካሂድ የቆየው ስድስተኛው ዙር “ይቆጥቡ ይሸለሙ” መርሃ ግብር መጠናቀቁን ምክንያት በማድረግ ዕጣ ለወጣላቸው ደንበኞቹ ያዘጋጃቸውን ሽልማቶች አስረከበ።
ሐሙስ ግንቦት 4 ቀን 2014 ዓ.ም በግዮን ሆቴል በተካሄደው የሽልማት አሰጣጥ ስነስርዓት ላይ ለዕድለኞቹ ሽልማቱን ተሰጥቷል።
በሽልማት አሰጣጥ ስነስርዓቱ ላይ እንደተነገረው በተለያዩ የስራ መስኮች ላይ የተሰማሩ ዜጎች ቁጠባን ባህል በማድረግ ህይወታቸውን እንዲያሻሽሉና በሃገር ኢኮኖሚ ግንባታ ላይ የራሳቸውን ሚና እንዲያሳርፉ ቡና ባንክ ልዩ ልዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተደራሽ ያደረገ የቁጠባ መርሃ ግብር ዘርግቶ ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል።
ከነዚህም መካከል በህዝብና ጭነት ማመላለሻ ትራንስፖርት ዘርፍ ላይ የተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ቁጠባን ባህል በማድረግ ህይወታቸውን እንዲያሻሽሉ በማሰብ የተዘጋጀው የቁጠባ መርሃ ግብር ለ6 ዙሮች ያህል ሲካሄድ ቆይቷል።
ቡና ባንክ በትራንስፖርት ዘርፍ ላይ ለተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ትኩረት ሰጥቶ አንድም የቁጠባ ባህላቸውን እያሳደጉ የባንክ አገልግሎቶች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ፣ በሌላ በኩልም በመቆጠባቸው ብቻ ተሸላሚ እንዲሆኑ የሚያስችላቸውን መርሃ ግብር በመቅረጽ የቅስቀሳ እና ግንዛቤ ማስጨበጫ ተግባራትንም ሲያካሂድ ሰንብቷል።
ባንኩ በአምስት ዙሮች ሲያካሂድ የቆየውንና በመደበኛና ሜትር ታክሲና ባለሶስት እግር ተሸከርካሪዎች ሹፌሮችና ባለንብረቶች ላይ ብቻ ተወስኖ የቆየውን የይቆጥቡ ይሸለሙ መርሃ ግብር በማስፋት ወደፈሳሽና ደረቅ ጭነቶች ማመላለሻ እንዲሁም አነስተኛ፣ መካከለኛ እና ከፍተኛ የህዝብ ትራንስፖርት ዘርፍ አሳድጎታል።
ይህም የቁጠባ መርሃ ግብር በአጠቃላይ የትራንስፖርት ዘርፍ ላይ የተሰማሩ ባለንብረቶችን፣ አሽከርካሪዎችን፣ ረዳቶችንና ሌሎች ድጋፍ ሰጪ አካላትን በማካተት የተሳታፊዎችን ቁጥር ለማሳደግ አስችሏል።
መርሃ ግብሩ ተሳታፊዎች በቡና ባንክ ቅርንጫፎች ሂሳብ ከፍተው የዚህ የልዩ ቁጠባ አገልግሎት ተሳታፊ ሲሆኑና በሂሳብ ቁጥራቸው ከ900 ብር ጀምረው ሲቆጥቡ የሽልማት ዕጣ ቁጥር የሚያገኙበትን አሰራር ዘርግቷል።
በዚህ 6ኛ ዙር የይቆጥቡ ይሸለሙ መርሃ ግብር ለዕጣው አሸናፊዎች የተዘጋጁት ሁለት የ2021 ሞዴል ዘመናዊ የቤት አውቶሞቢሎች፣ ሁለት ባለሶስት እግር ተሽካርካሪዎች፣ አምስት የልብስ ማጠቢያ ማሽኖች፣ አምስት ዘመናዊ ማቀዝቀዣዎች፣ አምስት 55 ኢንች ቴሌቪዠኖች፣ አምስት የውሃ ማጣሪያዎች እና አስር ስማርት የሞባይል ስልኮችም በይፋ ለእድለኞች ተበርክተዋል፡፡ ባንኩ በአጠቃላይ በዚህ መርሃ ግብር ተሳታፊ ለሆኑ 34 ደንበኞቹ ሽልማት ሰጥቷል።
ቡና ባንክ ላለፉት 12 ዓመታት ቁጠባን ባህል ያደረገ ህብረተሰብ እንዲፈጠር ባደረገው ጥረት ከ1.9 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችን በማፍራት ጠንካራ ማህበራዊ መሰረት መገንባት ችሏል።
ከግለሰቦች ህይወት ማሻሻል ባሻገር ለሃገር ኢኮኖሚ ግንባታ መሰረታዊ ሚና እንደሚጫወት የሚታመነው ቁጠባ በህብረተሰቡ ዘንድ ባህል እንዲሆን ለማስቻል ቡና ባንክ በየጊዜው የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተደራሽ የሚያደርጉ አዳዲስ የቁጠባ ፕሮግራሞችን ከማበረታቻ ሽልማቶች ጋር በመዘርጋት ከፍተኛ ቁጥር ያለውን የማህበረሰብ ክፍል የባንክ ተጠቃሚ ማድረግ ችሏል ።
የኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት ነው የሚባለው የትራንስፖርት ዘርፍ የሃገራችን ምጣኔ ሃብት እጅግ አስፈላጊ አካል ከመሆኑ ባሻገር የልማትና ዕድገት ማሳለጫ አይነተኛ መሣሪያም ጭምር ነው።
የትራንስፖርት መሠረተ ልማት መስፋፋት ከከፍተኛ የእድገት ደረጃዎች ጋር የተቆራኘ እንደመሆኑ የትራንስፖርት ሥርዓቶች ቀልጣፋ ሲሆኑ ለተሻለ የገበያ ተደራሽነት ፣ ለበርካታ የሥራ ስምሪት እና እንደተጨማሪ ኢንቨስትመንቶች ላሉ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ዕድሎች እና ጥቅሞች በር ይከፍታል።
ቡና ባንክ የዚህን ዘርፍ ተዋናዮች ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል የቁጠባና ሽልማት መርሃ ግብር በመዘርጋት የበርካታ ደንበኞቹን ህይወት መቀየርም ችሏል፡፡
በመርሃ ግብሩ ማጠቃለያ ላይ ለዕጣ አሸናፊዎቹ የተዘጋጁት ሽልማቶች ተበርክተዋል።
ከተቋቋመ 12 ዓመታት ያስቆጠረው ቡና ባንክ በመላው ሃገሪቱ 338 ቅርንጫፎች ያሉትና በየጊዜው አዳዲስ ደንበኞችን በማፍራት የደንበኞቹን ቁጥር ከ 1.9 ሚሊዮን በላይ ማድረስ የቻለ የግል ባንክ ነው።
የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ያማከለ፣ ፍላጎትና አቅማቸውን ያገናዘበ የልዩ ቁጠባና ብድር አገልግሎቶችን በማመቻቸትም በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎችን ወደባንክ አገልግሎት ማምጣት ችሏል።