• ስምምነቱ የተፈረመው ከገቢዎች ሚኒስቴር እና ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር ነው
በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ከዛሬ 4 ዓመት በፊት ያበለጸገው “ደራሽ” የተሰኘ የኤሌክትሮኒክስ መላ የግብር አከፋፈል ስርዓት ከሰው ንክኪ ነጻ በሆነ መንገድ እንዲከናወን ለማስቻል ያለመ ቢሆንም እስካሁን ድረስ በዚህ ዘዴ ተጠቅመው ግብር የሚከፍሉ ግለሰቦች ቁጥር ገና ከ13 ሺህ 796 ነው።
ከ16 ሺህ ጥቂት ከፍ የሚሉ ግለሰቦች ደግሞ መረጃዎቻቸውን በኤሌክትሮኒክስ ስርዓት ላይ ያስገቡ ቢሆንም ገና ወደክፍያ ስርዓቱ አልገቡም። ለዚህ አንዱ ምክንያት ደግሞ የክፍያ ስርዓቱ ከባንኮች ጋር የተሳሰረ ባለመሆኑ ነው ይላሉ የገቢዎች ሚኒስቴር ሚኒስትር ዲኤታ ወይዘሮ መሰረት መስቀሌ።
ይህንን የኢ-ታክስ ክፍያ አሰራር ከባንኮች ጋር ለማስተሳሰር የተጀመረውን ተግባር በሚፈለገው ፍጥነት ለማጠናቀቅ አንዱ እንቅፋት ለአሰራሩ ቀልጣፋነት አጋዠ የሚሆን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሊጂ መሰረተ ልማት ያሟሉ ባንኮች በቁጥር ጥቂት ሆነው መገኘታቸው መሆኑን ሚኒስትር ዲኤታዋ ይገልጻሉ።
ሚኒስትሯ እንዳስታወሱት እስካሁን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ጨምሮ ይህንን ስርዓት ተቀብለው የመተግበር አቅም ያዳበሩ ባንኮች ስምንት ሲሆኑ ከነርሱም ጋር የሶስትዮሽ ስምምነት ተፈርሟል ።
እነሆ ዛሬ ደግሞ ቡና ባንክን ጨምሮ ደቡብ ግሎባል ባንክ እና እናት ባንክ ለዚህ አሰራር ብቁ ሆነው በመገኘታቸው አገልግሎቱን ለመጀመር የሚያስችላቸውን የሶስትዮሽ ስምምነት ከሚኒስቴሩ እና ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር ተፈራርመዋል።ይህ ሲጨመር እስካሁን ስምምነቱን የፈረሙት ባንኮች ቁጥር 11 ደርሷል።
በፊርማ ስነስርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የቡና ባንክ ቺፍ ኮርፖሬት ሰርቪስ ኦፊሰር አቶ ሙሉነህ አያሌው እንዳሉት ቡና ባንክ የፋይናንስ ስርዓቱን ዲጂታይዝ በማድረግ የሃገርን የገቢ አሰባሰብ ስርዓት ለማቀላጠፍ ሙሉ ዝግጁነት አለው።
ባንኩ ደንበኞች ጊዜያቸውን ቆጥበው ሳይጉላሉ ባሉበት ስፍራ ሆነው በኤሌክትሮኒክ ዘዴ ግብር እንዲከፍሉ ለማስቻል ባንኩ የሚጠበቅበትን ሁሉ ይወጣል ነው ያሉት አቶ ሙሉነህ።
ዛሬ ሃምሌ ቀን 2014 ዓ.ም በገቢዎች ሚኒስቴር በተካሄደው በዚሁ የሶስትዮሽ ፊርማ ስነስርዓት ላይ ሌሎች ባንኮችም በዚህ ስርዓት ውስጥ ለመግባት የሚያስችላቸውን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሊጂ ስርዓት በማዘመን አሰራሩን እንዲቀላቀሉ ጥሪ ቀርቧል።
ስምምነቱ የቡና ባንክ እና ሌሎች የስምምነቱ ፈራሚ ባንኮች ደንበኞች በኤሌክትሮኒክስ መላ ባሉበት ሆነው ግብር ለመክፈል የሚያስችላቸውን ዕድል ይፈጥራል።